
ከዚህ ቀደም የደረሰኝ ህትመት ጥያቄ ማቅረብ የሚቻለው እስከ ጥር 30 ቀን 2017 ዓ.ም ብቻ መሆኑ በተገለጸው መሰረት ቁጥራቸው 45,226 የሆኑ ግብር ከፋዮች የህትመት ጥያቄ ማቅረብ መቻላቸውን የገቢዎች ሚኒስትር ክብርት ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሤ ከክልል እና ከተማ አስተዳደር የገቢ ዘርፍ አመራሮች ጋር በበይነ መረብ ባደረጉት ውይይት ገልጸዋል፡፡
ሆኖም በተለያዩ ምክንያቶች የህትመት ጥያቄያቸውን ያላቀረቡ ግብር ከፋዮች መኖራቸውና ይህን ታሳቢ በማድረግ የህትመት ጥያቄ ማቅረቢያ ቀነ ገደብ እስከ የካቲት 30 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ እንዲራዘም በውይይቱ ተወስኗል፡፡
እንደ ሀገር በገቢው ዘርፍ የሚሰተዋሉ ክፍተቶችን ለማረም በርካታ የሪፎርም ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ክብርት ሚኒስትር ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሴ በውይይቱ የገለጹ ሲሆን በተለይም የማንዋል ደረሰኝ አጠቃቀም እና አስተዳደር ስርዓትን በማሻሻል የሚፈለገውን የገቢ ዕድገት ማስመዝገብ ያሰፈልጋል ብለዋል፡፡
ልዩ መለያ ኮድ (QR Cod) የተካተተበት ሚስጥራዊ የደረሰኝ ህትመት ሥርዓትን ወደስራ ማሰገባት የሚያስፈልግ መሆኑን ያስገነዘቡት ሚኒስትሯ እስከ አሁን ባለው አፈፃፀም ውጤታማ ስራዎች ተሰርተዋል ሲሉ ተናግረዋል፡፡